tg-me.com/orthodox1/13095
Last Update:
☞ ያእቆብ ከዚሁ ቦታ ተነስቶ ወደላባ ሄደ ላባ የናቱ ወንድም አጉቱ ነው። በመንገዱም የበጎች ዓዘቅት ጉድጓድ አየ። ይህም ዓዘቅት በከባድ ድንጋይ የተዘጋ ነበር። በቀላሉ ለመክፈት አይቻልም ነበር። የላባ ልጅ ራሄል ከዚያ ቁማ ነበር። (በጎቿን ለማጠጣት) ያዕቆብ የውኃውን ጉድጓድ የተከደነበትን ድንጋይ ከፈተና የውሃ መቅጃ ከራሄል እጅ ተቀብሎ በጎቹን ከጉድጓዱ ውሃ በመቅዳት አጠጣቸው በጎቹን አጠጥቶ ሲያበቃ ያዕቆብ ራሄልን ተመለከታት ወደሷም ቀርቦ ሳማት። ያዕቆብ የውሃውን ጥልቅ ጉድጓድ መክፈቱ የቅድስት ጥምቀት ምሳሌ ነው የጥምቀት ምስጢር ረቂቅ ነውና ።
✧ ለቡኬ ኦ ወልድየ ቀሌሚንጦስ ከመ ኢክህለ ያዕቆብ ይስዓማ ለራሔል ዘእንበለ ዳእሙ እምድኅረከሰተ አፉሃ ለዓዘቅት ወአስተየ አባግዓ እምኔሃ ወከማሁ ይቤ አነኒ ኢርቱዕ ለሕዝብ ይባኡ ቤተ ክርስቲያን እንበለይጠመቁ እስመ እምድኅረ ተጠምቁ ይከውኑ አበግዒሁ ለክርስቶስ።
☞ ልጄ ቀሌሚንጦስ ሆይ የውሃውን ጥልቅ ጉድጓድ ከፍቶ በጎቹን ከማጠጣቱ በፊት ያዕቆብ ራሄልን ሊስማት አልቻለም የጥልቅ ጉድጓዱን መክደኛ ከፍቶ በጎቹን ካጠጣ በኋላ ግን ራሄልን ሳማት እኔም የዚሁን ምሳሌ እነግርሃለሁ ሰዎች በቅድስት ጥምቀት መንፈስ ቅዱስን ሳይቀበሉ ወደቅድስት ቤተክርስቲያን መግባት ክልክል ነው። በጥምቀት የክርስቶስ በጎች ይሆናሉና።
የጥልቅ ጉድጓዱ መክደኛ መርገምን፣ ያዕቆብ ክርስቶስን፣ ውኃው ጥምቀትን፣ በጎቹ ምእመናንን መስለው መተርጎማቸውን ልብ ይሏል!
አበ ሊቃውንት ቅዱስ ያሬድም ወብዙኃን ባለው የቀበላ ዝማሬው ይህን እንዲህ በማለት ተርጉሞልናል፦
✧ ወብዙኃን ኖሎት መጽኡ ወስዕኑ ከሢቶታ ለዕብን እምአፈ አዘቅት እስከ ይመጽእ ያዕቆብ ዘክቡት ውስተ ሐቌሁ ዘሀሎ ይሠጎ እምሰብእ ከሠተ ወአስተየ መርዔቶ ወከማሁ መጽኡ ብዙኃን ነቢያት ወስዕኑ ከሢቶታ ለጥምቀት እስከ ይመጽእ ዓቢይ ኖላዊ እምሰማይ ከሠተ ወአጥመቀ ብዙኃነ አሕዛበ በውስቴታ መንክር ተአምሪሁ ለመድኃኒነ በከመ ወጽአት በትር እምሥርወ ዕሤይ በአምሳለ በትረ ያዕቆብ በዘይርዒ አባግዒሁ ይእቲኬ ማርያም ይእቲ ወበእንተ ዘይቤ ትወጽእ በትር ወየዓርግ ጽጌ ውእቱኬ ዋህድ ውእቱ ውእቱኬ ወልደ አምላክ ውእቱ።
[ብዙ እረኞች መጡ ከጉድጓዱ አፍ ላይ የተገጠመችዋን ድንጋይ ለማንሳት አልቻሉም ሰው ይሆን ዘንድ ያለው በወገቡ ያለ ያዕቆብ እስኪመጣ ድረስ። እሱ ከፍቶ በጎቹን አጠጣ እንደዚሁ ብዙ ነቢያት መጡ ጥምቀትን መግለጥ አልቻሉም ዓቢይ ኖላዊ ከሰማይ እስኪመጣ ድረስ። እሱ ጥምቀትን ገለጠ በውስጧ ብዙ አሕዛብን አጠመቀ። የመድኃኒታችን ምልክቱ የሚያስደንቅ ነው ከዕሤይ ሥር በትር እንደወጣች፤ በጎቹን በሚጠብቅበት በያዕቆብ በትር አምሳል፤ ይህችውም ማርያም ናት በትር ትወጣለች አበባውም ከፍ ከፍ ይላል ማለቱ ወልድ ዋህድ ነው። እርሱ የአምላክ ልጅ ነው።]
፪ኛ】 በዘፍጥረቱ ትርጓሜ ላይ ያዕቆብ በላባ ቤት ስለ ራሔልና ልያ ፲፬ ዓመታት ተገዝቶ አገልግሏል። “ወይእዜኒ ማዕዜኑመ አንሰ እገብር ቤተ ለርእስየ? ☞ እኔ ደግሞ ለቤቴ የምሠራው መቼ ነው?” 【ዘፍ. ፴፥፴】 ሲል ጠይቆ ንብረት ተካፍሎ ተለይቷል። ከሚጠብቀው መንጋም ሽመልመሌ ዝንጉርጉሩን ለራሱ ሲያደርግ ከሚወለዱትም መኃል ያን የመሰለውን እንዲወስድ ላባ ፈቅዶለታል።
በዚህ ጊዜ ያዕቆብ እንዲህ አደረገ ዘፍጥረት ፴፥፴፯–፵፪
" ያዕቆብም ልብን ለውዝ ኤርሞን ከሚባሉ እንጨቶች እርጥብ በትርን ወስዶ በበትሮቹ ውስጥ ያለው ነጭ እንዲታይ ነጭ ሽመልመሌ አድርጎ ላጣቸው። የላጣቸውንም በትሮች በጎቹ ውኃ ሊጠጡ በመጡ ጊዜ በውኃ ማጠጫው ገንዳ ውስጥ በበጎቹ ፊት አኖራቸው፤ በጎቹ ውኃ ሊጠጡ በመጡ ጊዜ ይጎመጁ ነበር። በጎቹም በትሮቹን አይተው ከመጎምጀታቸው የተነሣ ፀነሱ፤ በጎቹም ሽመልመሌ መሳይና ዝንጕርጕር ነቍጣም ያለበቱን ወለዱ። ያዕቆብም ጠቦቶቹን ለየ፥ ሽመልመሌ መሳይና ጥቁር ያለባቸውን በጎቹንም ሁሉ በላባ በጎች ፊት ለፊት አኖረ፤ መንጎቹንም ለብቻቸው አቆማቸው፥ ወደ ላባም በጎች አልጨመራቸውም። እንዲህም ሆነ፤ የበረቱት በጎች በጎመጁ ጊዜ፥ በጎቹ በትሮቹን አይተው በበትሮቹ አምሳል ይፀንሱ ዘንድ ያዕቆብ በትሮቹን በውኃ ማጠጫው ገንዳ ውስጥ ከበጎቹ ፊት አደረገ፤ በደከሙ በጎችም ፊት በትሩን አያደርገውም ነበር፤ የደከሙትም ለላባ፥ የበረቱትም ለያዕቆብ ሆኑ።"
ታሪኩ በጥላነት የያዘው ምሥጢርና በምሳሌነት የሚያስተምረንን አማናዊ የምሥጢረ ጥምቀት ፍቺ መተርጉማን እንደሚከተለው አመሥጥረውልናል
☞ አብትር (በትሮቹ) የሦስቱ አካላት ፣ የተላጡት የአብ የመንፈስ ቅዱስ ፣ ቅጥልጣል የሆነው የወልድ አምሳል [አምላክ ወሰብእ ነውና] ፣ አባሕኵ የመምህራን፣ አባግዕ የምእመናን፣ ውኃ የጥምቀት፤
☞ አባግዕ አብትርን እየመሰሉ መወለዳቸው ፦ ምእመናንም በጥምቀት ምክንያት ሥላሴን መስለው ይወለዳሉና፤
☞ ላባ የዲያብሎስ፣ ያዕቆብ የጌታ ምሳሌ፤
☞ ምልክት ያለው ለያዕቆብ፣ ምልክት የሌለው ለላባ እንደሆነ፦ ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ያለው ለጌታ እንዲሁም ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና የሌለው ለዲያብሎስ ሁኗልና፤
ይኽነረኑ ይዞ የመልክዓ ሥላሴ ደራሲ በምሥጢር አስማምተው እንዲህ ብለዋል
ሰላም ለአዕዛኒክሙ አናቅጸ ጸሎት ሠናይ
ምሥጢራተ ሰሚዕ ሥላሴ ዘይተልዎ ርእይ
በአብትረ ያዕቆብ በርሃ ሥላሴክሙ ፀሐይ
ወተመሰሉ ሰብአ ዓይን አባግዓ ላባ ወማይ
ለኀበ አባግዕ ዘዮም ወጥምቀት ዓባይ
☞ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ሆይ፤ ርዕይ የሚከተለው ምሥጢራትን ለሚሰማ የበጎ ጸሎት በር ለሆነ መለኮታዊ አእዛናችሁ (ዦሮዎቻችሁ) ሰላምታ ይገባል። ሥሉስ ቅዱስ ሆይ፤ የሦትታችሁ ፀሐይ በያዕቆብ በትሮች ላይ አበራ። ስለሆነም ለአሁኑ የታላቂቱ የጥምቀት ልጆች የቀድሞ የላባ በጎችና የሚጠጡበት የወንዝ ውሀ መልካም ምሳሌ ሆኑ።
ከዚህ ባሻገር በዛሬውም ቅዳሴ በዓሉን በሚመለከት የተሰበከው ቃለ ዳዊት ካነሳነው ምሥጢር ጋር በተገናኘ እንዲህ የሚል ነበር ፧
ወምስካይነ አምላኩ ለያዕቆብ
ንዑ ትርአዩ ግብሮ ለእግዚአብሔር
ዘገብረ መንክረ በዲበ ምድር
☞ (የሠራዊት ጌታ ከእኛ ጋር ነው) የያዕቆብ አምላክ መጠጊያችን ነው። የእግዚአብሔርን ሥራ፥ በምድር ያደረገውንም ተኣምራት እንድታዩ ኑ። 【መዝ ፵፮፥፯】
አስቀድሞ በያዕቆብ ወልደ ይስሐቅ ላይ አድሮ ፣ ኋላ በገሊላ ቃና በሰርግ ቤት በአካል ተገኝቶ ፣ በየዘመናቱም ወደ ፍጥረቱ ጠባቂ መልአኩን ቅዱስ ሚካኤልን ልኮ… ድንቅ ድንቁን ታላላቅ መንክራት ያደረገ የያዕቆብ አምላክ እግዚኣ ኃያላን
✧ ተግባራቱን የምሥጢረ ጥምቀት ምሳሌ ካደረገለት ከቅዱሱ ያዕቆብ፣
✧ ከልጅነቱ ጀምሮ ያዕቆብን ከታደገውና ካዳነው ከቅዱስ ሚካኤልና
✧ ከበዓለ ቃና ዘገለሊላ ረድዔት በረከት ሁላችንን ያሳትፈን 🙏
እንደ ያዕቆብ መከራና መገፋት ለሚፈራረቅባት ተዋህዶ ሃይማኖታችና በውስጧ ለተጠለልን ምእመናን እውነተኛውና ብቸኛው ንጉሠ ነገሥት ክርስቶስ #በፍርዱ እስኪገለጥ ዋጋ እንዳናጣና እንዳንናወጽ #መቻል ያድለን።
✍️ ቃናዘገሊላ ፳፻፲፮ ዓ.ም. ደቡብ ሱዳን ጁባ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤ/ክርስቲያን የተጻፈ
BY ኦርቶዶክስ ተዋህዶ - 🇴🇷🇹🇭🇴🇩🇴🇽 🇹🇪🇼🇦🇭🇩🇴
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 283
Share with your friend now:
tg-me.com/orthodox1/13095